በመንግስት ልማት ድርጅት ይዞታና አስተዳደር የኢንስቲትዩቱ 2017 በጀት ዓመት የመጀመሪያ ሩብ ዓመት ሪፖርት ግምገማ ተካሄደ

አንጋፋው የብሔራዊ እንስሳት ጤና ጥበቃ ኢንስቲትዩት ገቢ ካለፈው በጀት ዓመት የተሻለ እንደሆነ ታየ

የመንግሥት የልማት ድርጅቶች ይዞታና አስተዳደር ተጠሪ ከሆኑ የልማት ድርጅቶች መካከል አንዱ እና በእንስሳት ክትባት ማምረት ዘርፍ በኢትዮጵያና  በአፍሪካ ደረጃ ግንባር ቀደም የሆነው የብሔራዊ እንስሳት ጤና ጥበቃ ኢንስቲትዩት የ2017 በጀት ዓመት የመጀመሪያው ሩብ ዓመት ዕቅድ አፈጻጸም ህዳር 17 ቀን 2017 ዓ.ም ተገመገመ፡፡

የብሔራዊ እንስሳት ጤና ጥበቃ ኢንስቲትዩት በሩብ ዓመቱ የኢንስቲትዩቱን የሥራ አፈጻጸም ለህዝብ በወቅቱ ይፋ ማድረጉ፣ያበለጸገውን አዲስ የመድኃኒት ምርት ለማስመዝገብ የሰነድ ዝግጅት እያደረገ መሆኑ፣የገበያ አመራር አጽድቆ እየሰራ መሆኑ እና  የ2016 በጀት ዓመት ሂሳብ ምርመራ ማጠናቀቁ በመልካም ጎን ከታዩ አፈጻጸሞች መካከል የሚጠቀሱ ናቸው፡፡

በሩብ ዓመቱ ግምገማ የኢንስቲትዩቱ የቦርድ ኮሚቴ አባላትና የማኔጅመንት አመራሮች፣የገንዘብ ሚኒስቴር የሚመለከታቸው የሥራ ኃላፊዎች፣ከአስተዳደሩ ኢንስቲትዩቱን የሚከታተሉ የሥራ ኃላፊዎችና ባለሙያዎች ተገኝተዋል፡፡ ግምገማው በኦፕሬሽን፣ በኮርፖሬት ገቨርናንስና ፋይናንስ፣በፕሮጀክት  እና በሪፎርም አፈጻጸም የተከናወኑ ተግባራት፣የታዩ ክፍተቶችና መሻሻሎች እንዲሁም የቀጣይ ትኩረት ጉዳዮች በስፋት ውይይት የተደረጉበት ነው፡፡

ኢንስቲትዩቱ በሩብ ዓመቱ ብር 85.38 ሚሊዮን ጠቅላላ ገቢ ያገኘ ሲሆን፣ይህ ካለፈው ተመሳሳይ በጀት ዓመት የ18.4 በመቶ ዕድገት አሳይታል፡፡ትርፍ ከግብር በፊት ደግሞ የብር 19.52 ሚሊዮን አፈጻጸም ተመዝግቧል፡፡አፈጻጸሙ ካለፈው በጀት ዓመት ተመሳሳይ ወቅት በ2.9 በመቶ ብልጫ አለው፡፡

የወጪ ንግድ ላይ ከሚሰሩ የልማት ድርጅቶች መካከል አንዱ ሲሆን ፣በሩብ ዓመቱ 92.49 ሺህ የአሜሪካን ዶላር ገቢ ማግኘት ችሏል፡፡ ኢንስቲትዩቱ በማህበራዊ አገልግሎተር ዕቅዱ መሰረት ለተለያዩ የማህበረሰብ ክፍሎች  የብር 550 ሺህ ድጋፍ አድርጓል፡፡ ከተሰብሳቢ ሂሳብ ደግሞ የብር 81.8 ሚሊዮን መሰብሰብ ችሏል፡፡ በግምገማው የሀብት ተመላሽ፣የጥቅል ትርፍ ህዳግ፣የአስተዳደራዊና የሽያጭ ወጪ ከገቢ ያለው ጥምርታ እና ሌሎች የፋይናንስ ጤናማነት መለኪያዎች ጋር በተገናኘ ግምገማው ትኩረት አድርጎ ውይይቶች ተካሒደዋል፡፡

የመንግሥት የልማት ድርጅቶች ይዞታና አስተዳደር ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ትዕግስቱ አምሳሉ ገቢ ከማመንጨት፣በሀገር ደረጃ የሌሉ እና በዘርፉ ለመስራት አጋዥ የሆኑ ፖሊሲዎች እንዲዘጋጁ ቀዳሚውን አስተዋጽኦ ከማድረግ፣ ከመድኃኒቶች ስርጭትና ከቦርድ አሰራር ጋር የተገናኙና ትኩረት የሚያስፈልጋቸው ጉዳዮች ላይ አጽንኦት ተሰጥቶ መሰራት እንዳለበት ጠቁመዋል፡፡

ውይይቱን የመሩት የመንግሥት የልማት ድርጅቶች ይዞታና አስተዳደር ተወካይ ዋና ዳይሬክተር አቶ ዝናቡ ይርጋ ኢንስቲትዩቱ ከዚህ በላይ አቅሙ ከፍ እንዲል እመንደሚፈለግና ትልቅ ሀገራዊ ፋይዳ ያለው ድርጅት እንደሆነ ገልጸው በቀጣይ ትኩረት ሊደረግባቸው በሚገቡ ጉዳዮች ላይ አቅጣጫ ሰጥተዋል፡፡

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *